አሜሪካ በርካታ አገራት ላይ አዲስ ታሪፍ ጣለች

የፎቶው ባለመብት, Getty Images
ባለፈው ዓመት ወደ ሥልጣን ከወጡ ወዲህ በድጋሚ የንግድ ጦርነትን ያቀጣጠሉት የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ፣ በ60 የአገሪቱ የንግድ አጋራት ላይ ታሪፍ ጣሉ።
አዲሱ ዙር እርምጃ የተካተቱትን ዩናይትድ ኪንግደም፣ ቻይና እና አውሮፓ ኅብረትን ጨምሮ በርካታ አገራት፣ ወደ አሜሪካ በሚልኳቸው ምርቶች ላይ ከ10 እስከ 12.5 በመቶ የሚደርስ ቀረጥ ይጠብቃቸዋል። ወደ አሜሪካ የሚገቡ ምርቶችን በሙሉ በሚባል ደረጃ ታሪፍ ተጥሎባቸዋል።
ይህ ታሪፍ ከዚህ ቀደም ትራምፕ የጣሉትን እና ተፈጻሚነቱ ዛሬ አርብ የሚያበቃውን ተመሳሳይ ቀረጥ ውሳኔ የሚተካ ነው። ትራምፕ ይህንን እርምጃ የወሰዱት እነዚህ ቁልፍ የኢኮኖሚ አጋሮች የጉልበት ብዝበዛን ለማስቀረት አልቻሉም በሚል ነው።
አሜሪካዊቷ የኢኮኖሚ ባለሙያ ካሮሊን ፍሬውንድ ግን ለእርምጃው የቀረበው ክስ ትራምፕ "ታሪፎቹን ለመጣል የሚያስችል ሕጋዊ ምክንያት ለመፈለግ" ሲሉ ያቀረቡት እንጂ “ለግዳጅ ሠራተኝነት ሲባል የተወሰደ አይደለም” ብለዋል።
የአሜሪካ ጠቅላይ ፍርድ ቤት በተያዘው የአውሮፓውያኑ 2026 መጀመሪያ ባስተላለፈው ውሳኔ፤ ከዚህ ቀደም የአደጋ ጊዜ አዋጅን በመጠቀም በዓለም አቀፍ ደረጃ የተጣለው ታሪፍ ሕገ ወጥ እንደሆነ ገልጾ ነበር።
ዋይት ሀውስ ባለፈው ወር ላይ የጉልበት ብዝበዛን ለማስቆም በቂ ሥራ አልተከናወነም የሚል ስጋት በማንሳት ከ10 እስከ 12.5 በመቶ ቀረጥ እንዲጣል ሀሳብ አቅርቦ ነበር።
የአሜሪካ የንግድ መስሪያ ቤት ተወካይ ጄሚሰን ግሪር፤ “የዛሬው እርምጃ የሰብአዊ መብት ጥሰት እና አሳሳች የንግድ ልምምድ ላይ የሚታየውን [ችግር] ማስተካከል” እንደሚጀምር ተናግረዋል። በዚህ ምክንያት “በሁሉም ቦታ የሚገኙ ሠራተኞችን ደህንነት ያሻሽላል” ብለዋል።
አዲሱ ቀረጥ በ60 የአሜሪካ የንግድ አጋራት ላይ የሚጣል ሲሆን የእነዚህ አጋራት ወደ አሜሪካ ከሚገባው ምርት ውስጥ 99.4 በመቶ እንደሚሸፍን ገልጸዋል።
በ’ዩሲ ሳን ዲዬጎ’ የዓለም አቀፍ ፖሊሲ እና ስትራቴጂ ትምህርት ቤት ዲን ፍሬውንድ ቀረጡን ለመጣል ስለቀረበው ምክንያት ከቢቢሲ ጥያቄ ቀርቦላቸዋል። የኢኮኖሚ ባለሙያዋ፤ “እንደማስበው፣ ታሪፍ ለመጣል ሕጋዊ እና እርምጃውን ለማስጠበቅ የሚያስችላቸው ምክንያት እየፈለጉ ነበር” ብለዋል።
“ምክንያቱም [የአሜሪካ የንግድ መስሪያ ቤት ተወካይ] ግሪር እና ትራምፕ በደንብ ግልጽ እንዳደረጉት ዋና ግባቸው ከንግድ ሚዛን ጉድለት ጋር የተያያዘ ነው። ለአሜሪካ ማኑፋክቸሪንግ ዘርፍ ሲባል ነው፤ ለጉልበት ብዝበዛ አይደለም” ሲሉም መልዕከታቸውን አብራርተዋል።



















